“የወይን ጠጅ እኮ የላቸውም!” (ዮሐ. 2፥3)
ይህን ቃል የተናገረችው የጌታ እናት
ቅድስት ማርያም ናት። የተናገረችውም በቃና ዘገሊላ ሰርግ ቤት እርስዋ፣ ልጇ ኢየሱስ ክርስቶስና ደቀ መዛሙርቱ ታድመው ባሉበት፣
ለሰርጉ የተዘጋጀው የወይን ጠጅ ባለቀ ጊዜ ነው። በብዙዎች ዘንድ ይህ የቅድስት ማርያም ቃል የእርሷ “ምልጃ” ተደርጎ እየታመነበትና
ስለ ምልጃዋ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ማስረጃ ተደርጎ እየተጠቀሰ ይገኛል።
በአንድ ወቅት ከነበሩ የቅዱስ ጳውሎስ
መንፈሳዊ ኮሌጅ የመጻሕፍት ተማሪዎች መካከል አንዱ ወደ መንደር ኼዶ ከወንጌላውያን አማኞች ጋር ስለ ማርያም ምልጃ ሲከራከር ቈይቶ
ወደ ኮሌጁ ይመለስና፣ ሌሎች ደቀ መዛሙርት ባሉበት ለመምህሩ ስለ ክርክራቸው ይነግራቸዋል። መምህሩም “ምን ጠቅሰህ ተከራከርህ?”
ይሉታል። ደቀ መዝሙሩም “የዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ ኹለትን ጠቀስሁላቸው” ብሎ መለሰላቸው። እርሳቸውም “ሰው ሳይጣላ ማስታረቅ አለ
ወይ? ማንና ማን ተጣልቶ ነው ይህን ስለ ምልጃ ማስረጃ ብለህ ያቀረብኸው? ሰዎቹ ከጌታ ጋር አልተጣሉ፤ ጌታ እንዲያውም የተጠራው
ወዳጅ ኾኖ ነው እኮ! ስለዚህ ይህን ስለ ምልጃ መጥቀስህ ልክ አይደለም” አሉት።